በእውነት ኢትዮጵያን እንመራለን የሚሉት ኢትዮጵያዊ ናቸውን?

sew


ንጉስ  ተስፋዬ

አስርት አመታት በላይ ኢትዮጵያውያንን እያስተዳዳረ ብቻውን ከሚያላዝንበት የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬድዮ  ውጭ ምድር ላይ የሚታየውና እውነተኛውን የኢትዮጵያ እውነታ ለተመለከተ እውነት ይህች ሃገር የምትተዳደረው በራስዋ በኢትዮጵያ ልጆች ነው ወይስ በሌላ? የሚል ጥያቄ እንዲከሁለት ጭር ቢያደርግ ሊገርመን አይገባም::

ሟቹ ጠ/ሚኒስቴር የስንቱን ኢትዮጵያዊ ህይወት በሰላም ማስከበር ስም፣ ባአሸባሪነት  ታርጋ፣  በምርጫ ሰበብ እና በሌሎችም የተለያዩ

ምክንያቶች የስንቱን ህይወት ቀጥፈውና አስቀጥፈው እሳቸው ወደ ማይቀርበት ቦታ ሄደዋል:: በምድር ፍርድ ቢያመለጡም በሰማይ ግን የሰራቸውን ዋጋ ያገኛሉ::

ህዝቡን እያስከፉ እና ድህነት ላይ ጥሎ፣ የስራ አጥ ቁጥር ከእለት እለት እየጨመረ፣  የፍትህ እጦት፣ የሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች እጦት፣ የስደቱ፣ የማስፈራራቱ ፣የእስሩ ፣የግድያውና እነዚህን ሁሉ መከራ ጭነውበት ኢትዮጵያዊ ነን ቢሉን ደንግጠን እርግጠኞች ናችሁ? ብንል ምኑ ይገርማል።

ኢትዮጵያዊ  ጀግኖችን የሚሳደብ፣ የሚያንቋሽሽ፣ እንመራዋለን የሚሉትን ህዝብ በአንድ  የ ቴሌቭዥን  ጣቢያ  ከባህላችን ውጭ በሆነ ነውር ቃላት ህዝብን የሚያንጓጥጥ፣ ኢትዮጵያን ያለ ባህር በር ያስቀረ፣ ምሁራንን የማይወድ፣ የራሱን ህዝብ የሚጠላ መንግስት በአለም የመጀመሪያው  ሊሆን  እንደሚችል ምንም ጥርጥር የለውም::

ውድ አንባቢያን በኢትዮጵያ ከ1997 ዓ ም ምርጫ በኋላ አንድም ቀን ሰላማዊ ሰልፍ ሊፈቀድ ቀርቶ ጀግኖች ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ድል አድርገው ሲመለሱ እንኳን ከኤርፖርት እስከ አ አ  ስታዲዮም በደስታና በእልልታ መቀበል የተከለከለበት ሃገር ከሆነ ቆየ ያም አልበቃ ብሎ በአመት አንድ ጊዜ የሚደረገውን ታላቁ ሩጫ“ 30 ብራችን ብሶት መግለጫችን“ ብለን እንዳንተነፍስ ከግማሽ በላይ የደህንነት ሃይል አብሮ በመሮጥ ንጹሃን ኢትዮጵያዊውን ከሩጫው በሁዋላ ወደ አዘጋጁት ያልታወቀ ማጎሪያ በመውሰድ ይገርፉታል፣ ያሰቃዩታል፣ ያሰፈራሩታል::

መቼም ይህን ሁሉ ጉድ የኢትዮጵያ ህዝብና ታሪክ አይረሳውም:: በኢትዮጵያ ምድር ኢትዮጵያዊያን ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ አትችሉም ተብለን ፊት ለፊት በራሳችን ቴሌቭዥን  ከተነገረንና ከተከለከልን ስንት  አመት ተቆጠረ? የሚገርመው የኤርትራን መንግስት ስርኣት የሚቃወሙት  ኤርትርዊያን ግን ያዉም በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ በሚደረግበት ወቅት በ አፍሪቃ አንድነት ድርጅት (OAU) በር ላይ  ድምጻቸውን አሰሙ:: እኔ ኤርትራዊያኑ ለምን ድምጻቸውን አሰሙ የሚል ተቃዉሞ  የለኝም ኢትዮጵያዊያን ለምን በሃገራቸው ድምጻቸውን ማሰማት ተከለከሉ ነው የኔ ጥያቄ::

ይህንን ባየን አመት እንኳን ሳይቆጠር ውድ የኢትዮጵያ ልጆች  የግራዚያኒን ሃውልት መሰራት በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ በወጡበት ዕለት ይኅው ፋሽስታዊ የኢትዮጵያ መንግስት እነዚህን ውድ ኢትዮጵያዊያውያኖች ወደ እስር ቤት ማጋዝ ጀመረ:: ታዲያ ኢትዮጵያን  የሚመሯት ኢትዮጵያዊያን ናችው ወይንስ ሌላ?

መቼም ኢትዮጵያዊ መሪ የግራዚያኒን ሃውልት መሰራት ራሱ ይቃወማል እንጅ  የተቃወሙትን ያገሩን ልጆች እያፈስ ወደ እስር ቤት አይውረውርም::

መንግስት ነኝ ባዩ ዝምታን በመረጠ ጊዜ ስለ ኢትዮጵያ ይመለከተናል ያሉን ሰዎች ለእስርና ለእንግልት ማብቃት ኢትዮጵያዊነት አይደለም ሊሆንም አይችልም::

በዚህ አጋጣሚ ለሰማያዊ ፓርቲና ለባለ ራእይ ወጣቶች ያለኝን አድናቆትና አክብሮት ሳልገልጽ አላልፍም ከስንት አመታት በኋላ እንደዚህ በድፍረት ለሃገርና ለመብት መቆም እንደሚቻል አሳይተውናል:: ለዚህ ትግላቸው ሌሎችም የተቃዋሚ ሃይሎች ከእነዚህ ወጣቶች ብዙ ብዙ መማርና ማወቅ ይገባችዋል እላለሁ:: ሌላው ለውድ ሙስሊም ወንድሞቻችን ያለኝ አክብሮት ላቅ ያለ ነው በሰላማዊ መንገድ እንዴት ድምጽን ማሰማት እንደሚቻል ለሁሉም ህዝብ ያሳዩና ያስተማሩ ናቸው:: እዚህ ላይ ሌላው መብቱ የተረገጠ ፣ድምጹ የተቀማ እና  በአጠቃላይ ሰብአዊ መብቱን የተነፈገ እንዲሁም የወያኔን ስርአት የምንቃወም፣ በተቃዋሚው ጎራ ያሉ አመራሮች እና ሌሎችቻችን ከእነዚህ ወንድሞቻችንና  እህቶቻችን ትልቅ ትምህርት ልንወስድ ይገባል እላለሁ:: ከአንድ አመት በላይ ተቃውሞቸውን እያሰሙና እጅግ ብዙ ፈተና በዚህ መንግስት እየደረሰባቸው ያንን ሁሉ ስቃይ እና መከራ በሰላማዊና እና በሰለጠነ መንገድ ተቃውሞቸውን እያሰሙ ያሉ ወገኖቻችን በመሆናቸው አሁንም ምስጋና  ይገባቸዋል::

ኢትዮጵያዊ በኢትዮጵያ ምድር መጻፍ ካልቻለ፣ መሰብሰብ ካልቻለ፣ ሃሳቡን በነጻነት መግለጽ ካልቻለ፣ መደራጀት ካልቻለ፣ መብቱን መጠየቅ ካልቻለ፣ በሃገሩ ተዘዋውሮ መስራት ካልቻለ፣ ንብረት ማፍራት ካልቻለ፣ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሃገሪቷ ላይ ባሉ በማንኛውም ሆቴሎች ውስጥ መሰብሰብ፣ መወያየት ፣ለፓርቲው የሚያስፈልጋቸውን የገንዘብም ሆነ የማቴሪያል ድጋፍ ማግኘት ካልቻሉ፣ እውን ኢትዮጵያን ኢትዮጵያዊ መሪ እያስተዳደራት ነው ወይ?

የኢትዮጵያን ለም መሬት ለአረብ፣ ለቱርክ፣ ለቻይ እና ለህንድ ባለሃብቶች  በአለም ታይቶ በማይታወቅ የረከሰ ዋጋ እየሸጠ ያለ መንግስት ቁራሽ መሬት ያለማን ኢትዮጵያዊ ደሃ ገበሬ በህገወጥነት ስም ሲያፈናቅለውና ንብረቱን እየነጠቀ ሲያሳድደው ወያኔና የእሱ አጨብጫቢዎች ግን ምንጩ ያልታወቀ ገንዘብ የሚጥሉበት አጥተው በየውስኪ ቤቱ ሲራጩበት ያድራሉ::

በሃይማኖት መሃል የሚገባ፣ እራሱ የመረጠውንና የራሱን ሃሳብ የሚያስፈጽመውን፣ እንዲሁም ለሆዱ ያደረውን ኣሽከር፣ በሃይማኖት ውስጥ የሚያስገባ፣  የአንድን ሃይማኖት ከሌላው ሃይማኖት አጋጭቶ እርሱ ትርፍ ለማግኘት የሚጥር፣ ተነግሮ የማያልቅ ግፍ የሚሰራው የወያኔ ቡድን የሚፈጽመው ግፍ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አልመጣም። በዛች ምስኪን ሳታጣ ባጣች ሃገር ላይ እንደመዝገር ተጣብቆ  እየመጠጣት የሚገኘው የወያኔ ጉጅሌ  በሀገር ውስጥ ስርአቱን የተቃወሙ ሰዎችን መሰብሰቢያ ቦታ በማሳጣት፣ እንዲሁም የተከራዩትን ሆቴል ይሁን አዳራሽ በመከልከል፣በማስከልከል ፣ተስብስቦ እንኳን  እራት መመገብ እንዳይቻል በማድረግ እጅግ በሚያሳፍርና በሚያሳዝን ደረጃ ላይ አድርሶናል::

በሰሜን አፍሪካ እና  በመካከለኛው ምስራቅ አረብ ሃገራት የተነሳውን የዲሞክራሲያዊ መብት ጥያቄ  አብዮት ያስደነገጠው የወያኔ ቡድን ከእቅዱ እና ከበጀቱ ውጭ አባይን እገድባለሁ በሚል ዕሳቤ  በከፍተኛ ድህነት ውስጥ የሚገኘውንና የሚላስ የሚቀመስ ያጣውን ህዝብ ለአባይ ግድብ ማዋጣት አለብህ እያለ  ቁም ስቅሉን እያሳየው ይገኛል::

አንባብያን ለዛሬ በዚች የመጨረሻ ሃሳቤን ልጠቅልል በሃገራችን ለሚደረገው የሰብአዊ መብት ረገጣ  የጊዜ ሁኔታ ነው እንጂ  ማንም ከተጠያቂነት አያመልጥም እንደ ጠቅላይ ምኒስትሩ ወደ ማይቀረው ሞት ቢኬድም በሰማይ ያለ አባት ለልጆቹ ከማንም በላይ ፍርድ ይሰጣል ከምድር ህግ ቢታለፍም ማለቴ ነው::

ሰማይና ምድርን ያለ ባላ ያቆመ

ቀንና ጨለማን የሚያፈራርቅ

ሁሉን ማድረግ የሚችል አምላክ

ኢትዮጵያን ለዘላለም ይጠብቅ!!!!

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/3018

Leave a comment